የኤሌክትሮኒክስ ትራንዛክሽ አዋጅ፣ የኤሌክትሮኒክስ ትራንዛክሽን ረቂቅ ደንብ እና የግል ዴታ ጥበቃ አዋጅ ዙሪያ ከግሉ ዘርፍ የዲጂታል ቢዝነስ አንቀሳቃሾች ጋር ውይይት ተደርጓል።
መድረኩ አዋጆችና ደንቦቹ ሲወጡ የሚመለከታቸው አካላት ግብዓት እንዲሰጡበት፣ በዘርፉ ያሉ ችግሮችን ለመለየትና የመፍትሄ ሃሳቦችን ለማስቀመጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነው።
የዘርፉ ተዋናዮች ከኤሌክትሮኒክስ ንግድ ጋር ተያይዞ ገቢዎች የዲጂታላይዜሽን ስራውን እንዲያፋጥን ጠይቀዋል።በተለይ ከኤሌክትሮኒክስ ደረሰኝና የኤሌክትሮኒክስ ታክስ ጋር ተያይዞ የተጠናከረ ስራ መስራት እንደሚጠይቅ አንስተዋል።

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ፕሮግራም ዳይሬክተር ጀነራል አብዮት ባዩ (ፒ ኤች ዲ) ዜጎች የዲጂታል አገልግሎት ላይ እምነት ኖሯቸው እንዲጠቀሙ ለማድረግ የህግ ማዕቀፎ እየተዘጋጁ ስለመሆናቸው አንስተዋል።
በኤሌክትሮኒክስ ንግድና የመረጃ ልውውጥ በወረቀት ከሚደረገው የመረጃና የገንዘብ ዝውውር እኩል እውቅና የሰጠ የኤሌክትሮኒክስ አዋጅ ፀድቆ ስራ ላይ ውሏል ብለዋል።
አሁን በረቂቅ ደረጃ ያለው የግል ዴታ ጥበቃ አዋጁ ግለሰቦች በግል መረጃቸው ላይ ያላቸውን ዝርዝር መብትና ጥበቃ የሚደነግግ ይሆናል።
የፀደቀው የኤሌክትሮኒክስ ትራንዛክሽን አዋጅ ደግሞ በኤሌክትሮኒክስ አማካኝነት የሚደረጉ የመረጃ ልውውጦች የሚመራበት የህግ ማዕቀፍ ሲሆን በኤሌክትሮኒክስ የተሰጠ መረጃ ከወረቀት እኩል ህጋዊ ያደረገ ነው።
አዋጁን ተከትሎ ደንብና መመሪያ የማርቀቅ ስራ እየተሰራ ይገኛል።