የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ከተባበሩት መንግሥታት የልማት ፕሮግራም ጋር በመተባበር ከሚኒስቴር መስሪያቤቱ: ከተጠሪ ተቋማት፣ ከክልል የሳይንስና ቴክኖሎጂ ቢሮዎችና ከተመረጡ የፌዴራል መስሪያ ቤቶች ለተውጣጡ ኃላፊዎች በኢኖቬሽን ስነ-ምህዳርና በቴክ-ኢንተርፕርነርሽፕ ዙሪያ የአቅም ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጥቷል::
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ባይሳ በዳዳ (ፒ ኤች ዲ) የኢኖቬሽን ስነ-ምህዳርን ማሳለጥ፣ ቴክኖሎጂዎችን ማልማት፣ ማላመድ፣ ማሳደግና በአግባቡ መጠቀም የሚያስችል አቅም ለመፍጠር ከተለያዩ ተቋማት ጋር በቅንጅት መሰራት እንዳለበት አስገንዝበዋል::
በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ ለመሰማራት ዝንባሌ ያላቸውን ጀማሪ ኢንተርፕራይዞችን በመደገፍ እያንዳንዱ ግለሰብ ኪስ የሚገባ ሀብት እንዲያገኝ የሚያስችል አቅም መፍጠር እንችላለን ብለዋል።
በማንኛውም ግለሰብ በማንኛውም ቦታ ሀገር ሊቀይር የሚችል የምርምርና የፈጠራ ስራ ካለው ተቋማችን ለመደገፍ ዝግጁ ነው ያሉት ሚኒስትር ዴኤታው በስልጠናው የተገኙ እውቀቶች በየተቋማቱ ወደ ተግባር ለመቀየር ሁሉም ሀላፊነቱን እንዲወጣ አሳስበዋል።እንደዚህ ያሉ ስልጠናዎች ከፍተኛ አቅም ስለሚፈጥሩ ለዘርፍ ተሳታፊዎች ተደራሽ እንዲሆኑ ተጠናክረው መቀጠል እንዳለባቸው ተጠቁሟል::