የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኢምባሲ ምክትል ሚሲዮን መሪ ዴቪድ ሬንዝ በተመራ የሴኔቱ ተመራጭ የደህንነት ኮሚቴ አባላት ጋር በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ዘርፍ በትብብር መስራት በሚቻልባቸው ጉዳዮች ዙሪያ መክሯል።
ሁለቱ ሀገራት በቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ተቋማቶቻቸው በጋራ መስራት በሚችሉባቸውና ዘርፉ ለአፍሪካ ኢኮኖሚ በሚኖረው አስተዋፅኦ ዙሪያ መክረዋል።
ኢትዮጵያ በለውጡ 3 አመታት ውስጥ ያስመዘገበቻቸው ድሎች፣ በዲጂታል ኢኮኖሚ ግንባታ፣ በዲጂታል ትራንስፎርሜሽን እቅድና በሳይንስ፣ ቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ፖሊሲ ክለሳ ዙሪያ ስለተሰሩና እየተሰሩ ስላሉ ጉዳዮች ለልዑካኑ ማብራሪያ ተሰጥቷቸዋል።
ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂ ዘርፍ ከአሜሪካ ጋር የመስራት ፍላጎት አላት ያሉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ አህመዲን መሀመድ (ፒ ኤች ዲ) የአሜሪካ ተቋማት በኢትዮጵያ ማዋዕለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ ጥሪ አቅርበዋል።
በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኢምባሲ ምክትል ሚሲዮን መሪ ዴቪድ ሬንዝ በበኩላቸው በቴክኖሎጂና ኢኖቬሽን ዘርፍ የአሜሪካ ተቋማት በኢትዮጵያ የመሰማራት ፍላጎት እንዳላቸው ገለፀዋል።
ኢትዮጵያና አሜሪካ የረጅም አመት ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ያላቸው ሀገራት ሲሆኑ ይህንን ግንኙነት በተለያዩ ዘርፎች ማጠናከር በሚቻልበት ዙሪያ ምክክር አድርገዋል።