በመድረኩ ኢትዮጵያን በመወከል የተሳተፉት የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ አህመዲን መሀመድ (ፒ ኤች ዲ) በኢትዮጵያ ምቹ የኢኖቬሽን ከባቢ ሁኔታን ለመፍጠር እየተሰሩ ስላሉ ስራዎች ማብራሪያ ሰጥተዋል።
የቴሌኮም ዘርፉን ወደ ግል የማዛወር ሂደት፣ የንግድና ኢንቨስትመንት ህግ ክለሳ፣ የኤሌክትሮኒክስ ትራንዛክሽን አዋጅ፣ የመረጃ ጥበቃ ፖሊሲ ስራዎች እንደተሰሩና ወደ የዓለም ኢኮኖሚ ውስጥ ለመግባት መደላድል እንደሚፈጥሩ ተናግረዋል።
የስታርትአፕ አዋጅ፣ የብሔራዊ የፈጠራ ስራ ፈንድ መቋቋም፣ ከባንኮች በቀላሉ ብድር ማግኘት እና የሥራ ፈጣሪዎች የውጭ ምንዛሬ የባንክ ሂሳብ እንዲኖራቸው የሚያስችሉ ስራዎች እየተሰሩ መሆናቸው ለጀማሪ የቴክኖሎጂ ስራ ፈጣሪዎች ኢትዮጵያ ተመራጭ እንድትሆን ያስችላታል ብለዋል።

ሚኒስትር ዴኤታው ከተሳታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎችም ማብራሪያ ሰጥተዋል። ለስራ ፈጣሪዎች ምቹ ሁኔታን መፍጠር፣ የገንዘብ ድጋፍ ማድረግ፣ ገበያን ማስፋትና የኮቪድ 19 ጫናዎችን ለመቀነስ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል።
እየተሰሩ ባሉ የማሻሻያ ስራዎች ለቴክኖሎጂ የስራ ፈጣሪዎች መጪው ጊዜ በኢትዮጵያ ብሩህ እንደሚሆን ተገልጿል።
በካናዳና፣ ሴኔጋልና ኢትዮጵያ በጋራ አዘጋጅነት እየተካሄደ ያለው አውደ ጥናቱ የካርቦን ልቀትን በመቀነስ የአየር ንብረት ለውጥን በመቋቋም ፈጠራ የታከለበት የኢኮኖሚ እድገት ለማምጣት የሚቻልባቸውን መንገዶች የሚፈትሽ ነው፡፡